2013 ጃንዋሪ 22, ማክሰኞ

የሻምፕዎን አቻ!

የሻምፕዎን አቻ!

ዛምብያ ልጆቹዋን ከአውሮፓ ሰብስባ፣
በካቻምናው ውጤት ጉራ ተጀብባ ፣
ታሪክ ባይኖራትም ከቁብ የሚገባ፣
ኢትዮጵያን ለመግጠም አለች ሜዳ ገባ።

አስር ሺዎች ሆኖ ደጋፊው ታጭቆ፣
በባንዲራ ቀለም ተቀብቶ ደምቆ፣
ለዋሊያ ሰጠው ደስታውን አሙቆ።

ጀማል ጥፋት ገጥሞት በቀይ ተሸኝቶ፣
አንድ ግብ ገብቶበት ዘሪውን ተዘናግቶ፣
ደጋፊው በንዴት ፍፁም ተቆጥቶ፣
ሳልሃድን ቅጣት ምት ሳያገባ ቀርቶ፣
ወደረፍት ውጡ ፍሽካውም ተነፍቶ።

በጥበቡ ብዛት ሰውን ያስደመመ፣
የዋልያ ቡድን በርጋታው ታደመ፣
መረበሽ መደንገጥ ፍጹም የሌለበት፣
መናበብ ቅብብል የተቀናጀለት፣
ያገሩ ገበሬ ሰውነት ወጣለት።

ተዘርቶ የበቀለ በአዋሳ ከነማ፣
ለጥቆም በጊዮርጊስ በጽኑ የለማ፣
ሰሞኑን በአጥቂነት ስሙ የገነነ፣
የአቻነት ግቡ ውጤቱን  አዳነ
ያን ሁሉ ደጋፊ ሆድ እንዳያባባ፣
አበስ አረገለት የደጋፊውን እንባ።

በአንዱ  ውድድር በጅምሩ ብቻ፣
ዋልያችን ሆኗል የሻምፕዎን አቻ!