2015 ኦክቶበር 8, ሐሙስ

ገፊና ተገፊ


ተገፊው መገፋት ልቡን አሳስኖት፣
ከፍ ወዳለው ሊሄድ ልቡ ተመኘበት፡፡

ገፊውም በፊናው 'ገፊ' ስሙን ጠልቶት፣
ዞር ሊል ተመኘ 'ገፊ' ወደማይሉት፡፡

የሰማዩ ጌታ የማይዘገይ አፍታ፣
ለማን ሰጠሁ ብሎ አይሰስት ለእፍታ

የየራሳቸውን ምኞት አርጐት እውነት፣
መገመት ባይችሉ አንዱ ያንዱን ፀሎት፣
እስኪያገኙት ድረስ ጓጉተው የተመኙት፣
ተገፋፍተውበት ፆሙን አሳደሩት፡፡

2015 ጁላይ 24, ዓርብ

ሞት እንደሌለ አየሁ

አባቴ ሁልጊዜ ኑርልኝ ከጐኔ፣
በክፍ በደጉ እንድትሆነኝ ወኔ፣
ስመረቅ ትምህርቴን እንድትኮራብኝ፣
ስዳር ስሞሸርም እንድትቆምልኝ፡፡

ልጆቼም ይምጡና ይቦርቁ ፊትህ፣
ልፊያቸውም ቻል እስኪዝል ጉልበትህ፣

ልጆቼንም ይዤ መርቀኝ ልምጣና፣
ሳስመርቅ ስድርም ባለም እቤቴ ና፡፡

መቼ ይጠገባል የወላጅ መኖሩ፣
ያሳቅቃል እንጂ የሞት ዙር ማክረሩ፡፡

ልጆቼ ጠየቁ መቼ ይመጣል አሉ፣
ሞተ’ እንዳልላቸው ጠጠረብኝ ቃሉ፤

በቃሉ ተምሬ ከሞት ወዲያ ህይወት፣
ተቀብዬው ኖሬ በልበ-ሙሉነት፣
ዛሬ ባንተ መሞት እምነቴ ሆነ እውነት፤

ከሞትክም በኋላ እንዳለህ ስላየሁ፣
አባቴ ባንተ ሞት - ሞት እንደሌለ አየሁ፡፡

ከሞትክም በኋላ እንዳለህ ስላየሁ፣
አባቴ ባንተ ሞት - ሞት እንደሌለ አየሁ፡፡

አባቴ በሞትህ ዛሬም ተምሬአለሁ፣
ፍቅርህን ሞተህም ዛሬም አየዋለሁ፣
የፍቅር መምህሬ እኔም ‘ወድሃለሁ፡፡