ክርክም እንደ አትክልት፣
ክርክም እንደ አፍሮ፣
በስግደት መከርከም፣
በጽሞና ማረም፣
በፆም ለመገረዝ፣
ይበቃል መደንዘዝ፣
በኑሮ ላይ መፍዘዝ፡፡
ደግሞም እንበል ቀና፣
ጨመር አርገንበት ፍቅርና ትህትና፣
ክርክም .. ክርክም … ክርክም ፣
የልቦናን ክፋት በፅሞና እክም፣
የትዕቢትን ነገር በፆም በማዳከም፣
የጉልበትን ግነት በስግደት ማለዘብ፣
ሰዋዊ ድግመትን በፆም መቀስ ክርክም፡፡
ሊገልህ ምሎ ቢቃጣ፣
አነጣጥሮ ሊስብ ቃታ፣
የሞት ብይን ላንተ ሰዶ፣
ክፉ ስሙን ልቡ ወስዶ፡፡
የነገር እጁን ላንተ ሲሰድ፣
ቃታና ጥይት ወዳንድ ኣይሄድ፣
አንዱን ስቦ ሌላን መስደድ፡፡
ጠላትህ
ራሱን ጠልቷል ካንተ በፊት፣
ነገር ይዞ … ሲፈተፍት፣
ሊያለብስህ ሲቸኩል አፈር፣
ልቡ በነገር ሲካረር፣
ነገር ቀምሞ ሲያድር፣
ቀኑ እያለፈ ባሻጥር፡፡
ጠላትህ
ምሬት ገብቶ ከልቡ ጥልቅ፣
ነገር ይዞ ሙጥኝ ባይለቅ፣
ጥላቻውን ቢያንቦረቅቅ፣
እንዳይከትህ ከነገር ጥልቅ፣
በእይታህ ከእሱ ልጠቅ፣
እርጋታህን ባክህ ጠብቅ፡፡
ጠላትህ
መስታውትህ ነው የራስ ማያ፣
የእልህ ስንቅ ማቀበያ፣
ያሸናፊነትህ መለኪያ፡፡
ፈጥሮታልና በመልኩ፣
ተስፋ አልቆረጠም አምላኩ፣
አያጠፋውም ጨርሶ፣
ልብም ያገኛል ተውሶ፡፡
ያኔ
ታዲያ … አንተም ፣
ተራህን ጠላት እንዳትሆነው፣
ብድር መላሽ ውሎ አድሮ፡፡
በደስታ በፍቅር አቅፈው፤
ያኔ
ይኼው ጠላት ወዳጅህ ነው፣
አምላክ ቀን ሰጥቶ የለወጠው፡፡
እናም
ጠላትህን በራሱ ጥል አትመዝነው፣
ለዚች ቀን ብድር ስጠው፣
በጠላህ ልክ አትጣላው፡፡